Tuesday, October 20, 2015

የሺዓና የአህሉሱና የዓሹራ ውሎ

የሺዓና የአህሉሱና የዓሹራ ውሎ

የዓሹራ ቀን፤ የፊዓአውንን ትእቢትና አምባገነነንነት ያከተመበትና ለሌሎችም መቀጣጫ የሆነበት፣ ነብዩላህ ሙሳም የተደሰቱበት ለአህሉሱና ታላቅ ትርጉም ያለው የድል ብስራት ቀን ነው። አህሉሱና ይህንን ቀን በአል አያደርጉትም። የተለየ ድግስም ሆነ አለባበስ የላቸውም። ሆኖም መልእክተኛው ﷺ በደነገጉት መሰረት ይፆሙታል፣ መልካም ተግባራትን ይፈፅሙበታል፣ ከአላህ ልዩ ምንዳን በመከጀልም በዒባዳ ያሳልፉታል።

ሺዓዎች ግን ስለ ዓሹራ ቀን ሲያስቡ ሚታወሳቸው የታላቁ ሰሀቢይ የአሊይ ኢብኑ አቢ ጣሊብ ልጅ ሁሰይን የተገደሉበት ቀን መሆኑ ብቻ ነው። ሺዓዎች በዚህ ቀን ሀዘናቸውን ለመግለፅ እራሳቸውን የሚጎዱ ብዙ ነገሮችን በስፋት ይፈፅማሉ። ጭንቅላትንና ሌሎች አካሎቻቸውን በስለት መብጣትና ማድማት (ተጥቢር)፣ ፊታቸውን መደብደብ (ለጥም፣) እራስን በሰንሰለት መግረፍና ማንገላታት፣ በእንብርክክ መሄድ፣ ብዙዎችም ዘንድ ጥቁር መልበስና የለቅሶ ሙሾ ማውረድ ብሎም በራስ ላይ ኩነኔን መጥራት የተለመዱ የአሹራ ትእይንቶቻቸው ናቸው።

በእጅጉ ይገርማል፤
ለኛ ለአህሉሱና ደስታን ሲያላብሰን፣ ተስፋን አሰንቆ ድልን ሲያበስረን፤ ለወንጀላችን ማርታን ለማግኘት  ሩጫ ውስጥ ሲከተን፤

ለሺአዎች ግና፤
የሀዘን የዋይታ፣ የውድቀት የሽንፈት ማስታወሻ፣ የተስፋ ማጨለሚያ ነው!!

ሁሰይን የነብዩ ﷺ የልጅ ልጅ በኢስላማዊ እውቀት ከመጠቁ ታላላቅ ሰሀቦች አንዱ ኗቸው። በኢባዳ ብርቱ የተወዳጇ የመልእክተኛው ﷺ ልጅ የፋጢማ ረዲየላሁ አንሀ ልጅ ናቸው። ስለዚህም ማንኛውም ሙስሊም በሁሰይን መገደል ሊያዝን ይገባል። ነገር ግን የሺአዎች አይነት የሀዘን መግለጫ መፈፀም ድንበር ማለፍ ነው። ኢስላማዊ መሰረትም የለውም፤ ብሎም የጃሂሊያ ቅሪት ነው። ዲናችን ይህንን አይነት ድንቁርና በግልፅ ለመከልከሉ ግልፅ መረጃዎች አሉን፤

عَنْ عَبْدِ اللَّهِ بن مسعود رَضِيَ اللَّهُ عَنْهُ قَالَ : قَالَ النَّبِيُّ صَلَّى اللَّهُ عَلَيْهِ وَسَلَّمَ : (لَيْسَ مِنَّا مَنْ لَطَمَ الْخُدُودَ وَشَقَّ الْجُيُوبَ وَدَعَا بِدَعْوَى الْجَاهِلِيَّةِ) رواه البخاري ومسلم

ከአብዱላህ ኢብኑ መስኡድ በተዘገበ ሀዲስ የአላህ መልእክተኛ ﷺ እንዲህ ብለዋል « "ሀዘንን ለመግለፅ" ጉንጩን የመታ፣ ልብሱን የተረተረ፣ እንደ ጃሂሊያ ሰዎች ሙሾ ያወረደ ከኛ አይደለም» ቡኻሪና ሙስሊም ዘግበውታል

ለሀዘን ሲል ፊቱን ወይም ደረቱን የመታ በዚሁ ውስጥ ይካተታል። ጉንጭን መመታት በሀዲሱ ላይ ተነጥሎ የተጠቀሰው በድሮ ጊዜ የተለመደ ስለነበር ብቻ ነው።
የጃሂሊያ ሰዎች ሙሾ፤ ሟችን በማሞካሸት ማስለቀስ እንዲሁም በራስ ላይ ጥፋትን እና ኩነኔን መመኘት ነበር።

ይህ የሺዓዎች የአሹራ ትእይንት አሹራ ከተደነገገበት መንፈስ የራቀና ኢስላም የማያውቀው የጃሂሊያ ርዝራዥ መሆኑ ግልፅ ነው።

☞ ይህንንም ከላይ ከጠቀስኩት መረጃ ባሻገር በተከታዮቹ ስድስት ነጥቦች ይበልጥ ግልፅ ማድረግ ይቻላል።

1) አሹራን ሺዓዎች በሚያሳልፉት መልኩ ማሳለፍም ይሁን የነሱን ተግባር መፈፀም በኢስላም የማይታወቅ ለመሆኑ ትልቁ መረጃ በታላላቅ ሰሀቦችና በምርጥ ተከታዮቻቸው ዘመን የማይታወቅ  በታሪክ ድርሳናት ሁሉ ያልተዘከረ መሆኑ ነው። ይህ ተግባር በሸሪዓችን የተደነገገና ምንዳን የሚያስገኝ ቢሆን ሰለፎች በቀደሙን ነበር።

የዚያን ጊዜ ዲን ያልነበረን ነገር አሁን ዲን ማድረግ ፈፅሞ አይቻልም!!

2) በኢስላም ውስጥ ብዙ ታላላቅ ሰዎች አልፈዋል። መልእክተኛው ﷺ በህይወት እያሉም ተወዳጇን ባለቤታቸውን ኸዲጃ ቢንት ኹወይሊድን አጥተዋል። እንደ ሀምዛ ቢን አብድልሙጠሊብ፣ ጃእፈር ኢብኑ አቢ ጣሊብ፣ አብዱላህ ኢብኑ ረዋሀህ እና ሌሎችም ብዙ የሚወዷቸው ታላላቅ ሰዎችም ተሰውተዋል። ነገር ግን ለአንዳቸውም ይህ አይነቱ የሀዘን ቀን አልደነገጉም። ታዲያ በእሳቸው ዲን ከተሟላ በኃላ ድንጋጌ ይመጣልን??

3) ሁለም ሺዓዎች የሁሰይን አባት ዓሊይ ከሁሰይን እንደሚበልጡ አይጠራጠሩም። ይህ ታላቅ ሰሀቢይ የኢስላም የቁርጥ ቀን ልጅ በ40ኛው የሂጅራ አመት በረመዳን ወር ሀያ ሰባተኛዋ ቀን በጁምአ ዕለት ለሰላተል ፈጅር ሲወጣ በግፍ ተገድሏል። ሺዓዎች ሆይ! እራሳችሁን የዓሊይ ጭፍሮች (ሺዓቱ አሊይ) ነን ትላላችሁ፤ ታዲያ ሁሰይን የተገደሉበትን ቀን የሀዘን ቀን ካደረጋችሁ አሊይ ኢብኑ አቢጣሊብስ የተገደሉበትስ?
ከዓሊይ ሁሰይንን አስበለጣችሁን??

4) ከዓሊይ በፊት ታላቁ ሰሀቢይ ኡስማን እና ኡመር በአሰቃቂ ግድያ ህይወታቸው አልፏል። ከሰሀቦች ሁሉ በላጭ የሆነውና ከነብዩ በኋላ በኸሊፋነት የመሩት አቡበከርም አልፈዋል። ነገር ግን ሰሀቦች ዘንድ ለማናቸውም ይህ አይነቱ የሀዘን ቀን አልተወሰነም።
ይሁንና ከሁሉ የከፋው አለማስተዋል፤ የነብዩን ﷺ ሞት መዘንጋታቸው ነው።  ይህ የሀዘን ስርአት ህጋዊ ነው ያለ ማንኛውም ሙስሊም ከነብዩ ﷺ ሞት የበለጠ ሊያሳዝነው የሚገባ ሀዘን የለም። በእውነትም ከእሳቸው ሞት የበለጠ አደጋ ይህንን ኡማ አልገጠመውም። የአላህ መልእክተኛ ﷺ እንዲህ ብለዋል፤
((إذا أصيب أحدكم بمصيبة فليذكر مصيبته بي فإنها أعظم المصائب)) رواه الطبراني والبيهقي والبغوي وصححه الألباني بمجموع طرقه في ((السلسلة الصحيحة)) (1106).
«ከናንተ አንዳችሁ ከባድ ሙሲባ ቢገጥመው በእኔ (መሞት) ምክኒያት የሚከሰተውን ሙሲባ ያስብ። ከሙሲባዎች ሁሉ ከባዱ እሱ ነው።» ጠበራኒይ አልበገዊና አልበይሀቂይ ዘግበዉታል። በተለያዩ የሚደጋገፉ የዘገባ ሰንሰለቶች የተዘገበውን ይህንን ሀዲስ ሸይኽ አልባኒ በ "ሲልሲለቱል አሀዲስ አሰሂሀህ 1106" ሰሂህ ብለውታል።

የታላላቆችን መሞት ወይም መገደል የሀዘን ቀን መሆን አለበት ካላችሁ፤

 ከነብዩ ﷺ ሁሰይንን አስበለጣችሁን??

5) የተፈፀመባቸውን ሰቆቃና በደል የምናነሳበት ገለፃ ክርስቲያኖች ነብዩላህ ኢሳ ላይ የደረሱ በደሎችን የሚገልፁበት አይነት መሆን የለበትም። የነሱ አካሄድ ማጋነን፣ ድንበር ማለፍና ደረሰ በሚሉት በደል ምክኒያት የአላህን ስልጣን ለኢሳ መስጠት ነው። የሺአም ግድፈት ለዚህ የቀረበ ነው። የሁሰይንን ሞት ብቻ ለይቶ ለሰው ልጆች የተፈፀመ መስእዋት እንደሆነ መደስኮርና ለሀጥያት ስርየት ብቸኛ ምክኒያት አድርጎ ማሰብ የሙስሊሞች እምነት ነውን?


6) ሙሰል'ሙሰዊ «አሺአህ ወተስሂህ» (ሺዓና ተሀድሶ) በሚለው መፅሀፋቸው፤ እራስን ማድማትና በሰይፍ መሰንጠቅ ወደ ኢራንና ኢራቅ ሺዓዎች ከህንድ የመጣባቸው የአምልኮ ስርአት ሲሆን የእንግሊዝ መንግስት ህንድና አካባቢውን በቀኝ ግዛት በያዘበት ወቅት ይህንን የአምልኮ ስርዓት ለማስፋፋት ከፍተኛ ጥረትና ድጋፍ ያደርግ እንደነበር አትተዋል። እንዲህ አይነቱ ተግባር የኢስላምን ውብ ገፅታ ስለሚያጠለሽ የኢስላም ጠላቶች በጣም እንደሚፈልጉት ግልፅ ነው። እስከመቼ ጠላት ምኞቱን በናንተ በኩል ያሳካል??

☞ ሺዓዎች ለነዚህ መጠይቆች ግልፅ ምላሽ የላቸውም። እንደውም የሚገርመው ዓሹራን በነሱ መንገድ በሀዘን ያላሳለፈን ሁሉ፤ በሁሰይን ሞት አላዘነምና የአህሉልበይት ጠላት (ናሲቢይ) ነው በማለት ይፈርጃሉ።

ዲናችን መረጃን እንጂ ለስሜታዊነት ቦታ አይሰጥም። አልሀምዱሊላህ!  ከማልቀስና ከማስለቀስ ባለፈ ታሪክን መርምሮ የዲንን መሰረቶችም ተገንዝቦ በብርሀን መንገድ ላይ መጓዝ መታደል ነው። በኢስላማዊ መርሆዎች በመወሰን ከእንዲህ አይነቱ የጃሂሊያ ተግባር መራቅ ፈፅሞ አህሉልበይትን መጥላት አይሆንም።  አህሉሱና በሁሰይን እና በሌሎች የነብዩ ﷺ ቤተሰቦች ላይ የደረሱ በደሎች ሁሉ ያወግዛሉ። መልእክተኛውም ቀደም ብለው ሁሰይንን መከራ እንደሚያገኘው ተንብየውለት ነበር። ነገር ግን በሌሎች የነብዩ ባልደረቦችም ላይ የከፉ በደሎች መድረሳቸው መዘንጋት የለበትም። ስለሁሉም እናዝናለን። ነገር ግን ሀዘን በዲናችን እራሱን የቻለ አካሄድ አለውና ከዛ አንወጣም።

ሺዓዎች ለሁሰይንም ይሁን ለሌሎች አህለልይት የአላህን ስልጣን መስጠታቸውንና ከርሱም ውጭ የድረሱለን ጥሪ በማሰማት ለቀብር በመስገድና ጠዋፍ በማድረግ ሽርክ መፈፀማቸውን በእጅጉ የሚወገዝ የሽርክ ተግባር ነው።

ውድ አንባቢ!
የሺአዎች እካሄድ ምን ያክል አመክኒዮ የጎደለውና ጭፍን
ውዴታን ወይም ጭፍን ጥላቻን ብቻ መሰረት ያደረገ መሆኑን ልብ በል!!

አላህ ከጥመት ይጠብቀን
አቡጁነይድ ሙሀረም 12/1436 ዓ.ሂ

1 comment: