Tuesday, September 1, 2015

አህባሾችና አላህን ከ‘ጂሀ’ እና ከ“መካን” የማጥራት እሳቤ

አህባሾችና አላህን ከ‘ጂሀ’ እና ከ“መካን” የማጥራት እሳቤ

ምስጋና ለአላህ የተገባ ነው። የአላህ ሰላምና እዝነት በመልእከተኛው ላይ የሁን። በመቀጠል፤

አላህ እንዲህ ብሏል፤
{الرَّحْمَٰنُ عَلَى الْعَرْشِ اسْتَوَىٰ} [طه : 5]
«አል ረህማን ከዓርሽ በላይ ከፍ አለ» ጣሀ 5

ለማንኛውንም ጤናማ ሙስሊም ይህንን አንቀፅ በመጥቀስ ለመሆኑ ይህንን አንቀፅ ስትሰማ፤ ‘ሰማያት አላህን ተሸክመዋል፣ ፍጥረራቱ ያካብቡታል’፣ ‘አላህ ከዓርሽ ፈላጊ ነው’ ወይም ‘አላህ በፍጥረታቱ ውስጥ ሰርጿል’ የሚሉ መጥፎ መልዕክቶችን ተረድተሀልን? ብለህ ብንጠይቀው፤ “ፈጽሞ አዕምሮዬ አላሰበዉም” እንደሚለን ግልጽ ነው።
 በፍልስፍና ልቡ ያልታወረ ማንኛውም ሙስሊም ይህንን እና መሰል መልእክቶችን ከጥመት በራቀ መልኩ እንደሚረዳው ግልጽ ነው።  በርግጥም ከዚህ ግልጽ ቁርአናዊ መልእክት ጥመትን የሚረዳ ልቡ ውስጥ በሽታ ያለበት ብቻ ነው። ስለዚህም አህሉሱና ግን አላህ ከእርሱ ክብርና ግርማ ሞገስ ጋር በሚሄድ መልኩ ከሰማያትና ከዓርሽም በላይ መሆኑን እና ከፍጥረታቱ የተለየ “ባኢን’ መሆኑን ያምናሉ።

በዚህ መልኩ ንፁህ ምልከታ ኖሮህ አላህ የተናገረውን አፅድቀህ ስትመሰክር፤ አህባሾችና ጥመትን ያወረሷቸው ቀደምት አንጃዎች «አላህ ከአርሽ በላይ ነው» ስትል በአላህ ክደሀል ይሉሀል። ለምን ብትላቸው ለአላህ ቦታ እና አቅጣጫን ስለሰጠህ ካፊር ይሉሀል። ስለዚህም ዘወትር "አላሁ መውጁዱን ቢላ መካን" የሚል ባዶ መፈክር ሀዲስ በማስመሰል ይደሰኩራሉ።

አህባሾች... የዚህን አንቀፅ ቀጥተኛ መልእክት በሰው አእምሮ የማይመጣን የጉድለት ባህሪ የሚያስገነዝብ የኩፍር መልእክት አድርገው ለምን ይረዱታል?  ሰሀቦችና ራቢዒዮች ከአላህ የመጣውን መልእክት ተቀብለው ሳይፈላሰፉ እንዳፀዱቀት አፅድቀው በማመን ፈንታ መካን እና ጂሀ የሚል ፀጉር ስንጠቃስ ለምን አስፈለጋቸው?
የነሱን መነሻና ትክክለኛውን የአህሉሱና አቋም ማወቅ ጠቃሚ ነውና ልብ ብለህ ተከታተለኝ።

በመሰረቱ "ጂሀ" እና "መካን" እነዚህ ቃላት ሸሪዓዊ መሰረት የላቸውም። ከዚህ ርዕስ ጋር በተያያዘ በቁርዓንም ይሁን በሀዲስ አናገኛቸዉም። በተመሳሳይ መልኩ ‘ሀድ’ እና ‘ጂስም’ የመሳሰሉ ጥቅል "ሙጅመል" ቃላት ሸሪዓዊ መሰረት የላቸውም። አህሉሱና በዚህም ይሁን በሌሎች ርዕሶች ላይ መረጃን መሰረት ያደረገ አካሄድ ስላላቸው እንዲህ አይነቶቹን ጥቅል ቃላት “አል አልፋዝ አል ሙጅመላህ” መነሻ አድርገው አይናገሩም መፈተኛ አያደርጓቸውም። ነገር ግን ከቢድዓ አራማጆች በኩል ሲመጡ ለማጽደቅም ይሁን ውድቅ ለማድረግ ሳይሽቀዳደሙ ቃሉን ባለበት በመተው የሚፈለግበት መልዕክት ምን እንደሆነ ይጠይቃሉ። ከምላሹም በመነሳት መልዕክቱ ሀቅ ከሆነ ያጸድቁታል፤ ሀቅ ካልሆነም ውድቅ ያደርጉታል።

ለምሳሌ፤ አንድ አህባሽ «ለአላህ ጂሀ ‘አቅጣጫ’ አታድርጉለት ይህ ኩፍር ነው» ቢልህ፤ ከዚህ ርዕስ ጋር በተያያዘ ‘ጂሀ’ የሚለውን ቃል በቁርአን እና በሀዲስ እንደማታውቀው በመንገር በዚህ ቃል ምን እንደተፈለገበት ጠይቀው። ሀሳቡ አላህ ከፍጡራኑ ሁሉ በላይ መሆኑን ማስተባበል ከሆነ ከቁርአንና ከሱና አረንዲሁም ከተፈጥሯዊ እምነት ጋር የሚጋጭ ተራ ወሬ መሆኑን ትነግረዋለህ። ነገር ግን የፍጥረተ ዓለሙ አካል የሆኑትን ስድስት አቅጣጫዎች ለአላህ መገለጫ ማድረግ የለብንም ለማለት ከሆነ ይህ የታወቀ እንደሆነ እና ይህ አይነት ትርጓሜ ያለዉን ‘ጂሀ’ ለአላህ እንደማናጸድቅ፤ ቀደወሞውንም ስለአላህ ስናወራ ዙሪያችን ያሉ አቅጣጫዎች ፍፁም እንደማይታሰቡን ታስረዳዋለህ።

{أَأَمِنتُم مَّن فِي السَّمَاء} [الملك : 16]

«ከሰማይ በላይ ያለውን ‘አላህ’ ትተማመናላችሁን?» አልሙልክ 16

ልብ በል ወንድሜ፤ ይህንን እና መሰል አንቀፆችን ሲሰሙ የቁርአንን መልእክት በቀጥታ በመጠምዘዝ ‘አላህ ከሰማይ በላይ’ መሆኑን ሲያስተባብሉ ታይና ተገርመህ ይህ ሁሉ ልፋት እና መወራጨት ምን አመጣው ብለህ ችግራቸውን ስታጠና፤ አሁንም ለአላህ ቦታ “መካን” መስጠት አይገባም የሚሉት የፍጡራን መኖሪያ የሆኑትን ሰባቱን የቅርብ ሰማያት በማሰብ እንደሆነ እንደዚሁ ‘አላህ ከፍጡራን በላይ ነው’ ሲባሉ በዙርያቸው የሚያውቋቸውን ስድስት አቅጣጫዎች በማሰብ አላህ ከጂሀ “አቅጣጫ” የጸዳ ነዉና ከፍጡራን በላይ ነው አይባልም እንደሚሉ ትረዳለህ። የስህተታቸው ሁሉ መሰረት ይህ ነው።

☞ ጀህሚያ፣ ሙዕተዚላ እንዲሁም አሻዒራ የአላህን የበላይ መሆን የሚያስተባብሉባቸው ፍልስፍናዊ መረጃዎች ሁሉ የሚያጠነጥኑት በዚህ ብዥታ ላይ ነው። መካን(ቦታ) እና ጂሀ(አቅጣጫ) ለአላህ አይገቡም በማለት የአላህን ከፍጡራኑ የበላይ መሆን ያስተባብላሉ። እውነታው ግን፤ እነሱ ለዚህ ስለ አላህ ባህሪያት ለማወቅ መነሻ ያደረጉት ከፍጥረተዓለሙ ጋር የተያያዙትን «ዉጁዲይ» ቦታ እና አቅጣጫን ነው። ስለ አላህ የሚነገሩ እውነታዎችን ሁሉ ፍጡራን ላይ በሚያያቸው ግንዛቤዎች ከሚተረጉም እውር አስተሳሰብ መጠንቀቅ ያስፈልጋል።

☞ አህሉሱና አላህ ከፍጡራን ሁሉ በላይ መሆኑን ያምናሉ፤ ‘ከሰማይ በላይ ነው’ ወይም ‘ከዓርሽ በላይ ነው’ የሚለዉን ሁሉ አላህ በነገራቸው መሰረት ሳይጨምሩና ሳይቀንሱ ይቀበሉታል። ስላልተነገራቸው የባህሪ ምንነት ‘ከይፊያ’ ግን ምንም አይናገሩም።  አህሉሱና ከአላህ ባህሪያት ጋር በተያዘ ፍጡራዊ የሆኑትን ጂሀ እና መካን ለአላህ አያጸድቁም።
ቁርአናዊውን የ‘ዑሉው’ አስተምህሮ ተቀብለው ሲያፀድቁም፤ ሙዓጢላዎች እንደሚያስቡት...

✘ አላህ አንደኛ ሁለተኛ ተብሎ በሚቆጠረው የመላዕክት መኖሪያ ሰማይ ላይ ይኖራል እያሉ አይደለም። መላዕክትም በሰማይ ሰዎች በመሬት በሚኖሩበት መልኩ አላህም በሰማይ ይኖራል የሚል እምነት ያለው ሰው በእርግጥም በአላህ ክዷል።

✘ እንደዚሁ ሰማይ አላህን ይሸከመዋል ወይም ያካብበዋል ከሚልም አስተሳሰብ የጸዱ ናቸው። ይህ የአላህን ከፍጥረታቱ ጋር መቀላቀልን “ሁሉል” የሚያምኑ የቢድዓ አራማጆች እምነት ነው።

✘ አላህ በፍጥረተዓለሙ ዉስጥ በሚገኙት ስድስት አቅጣጫዎች ይገለጻል፤ ፍጥረተአለሙም ያካብበዋል ማለትን ፈፅሞ አያመላክትም። ይህንን ያለ ሰውም በአላህ ላይ ውሸትን ተናግሯል፣ መንገድንም ስቷል።
አህሉሱና ይህ ሁሉ ጥመት ስለመሆኑ አይወዛገቡም።
የአላህ ከፍጥረታት በላይ መሆን አላህ በተፈጥሮ በልባችን ያኖረው ግልጽ እምነት ነውና። አላህ በቁርአን እንደገለፀው የአላህን ከፍጥረታት በላይ መሆን "ዑሉው" መግልጽ ብቻ ለአህሉሱና በቂ ነው።  በቁርአንም ላይ የምናገኘው አካሄድ ይኸው ነው። ‘አላህን ከጉድለትና ከመመሳሰል ማጥራት’ ጥቅል በሆነ መልኩ ሲቀርብ ፤ የአላህን ባህሪያት ማጽደቅ ግን በዝርዝር ሲቀርብ እናገኛለን። ለአብነት ያክል ተከታዩን መልእክት እናስተውል፤

لَيْسَ كَمِثْلِهِ شَيْءٌ ۖ وَهُوَ السَّمِيعُ الْبَصِيرُ} الشور : 11
 ‹‹የሚመስለው ምንም ነገር የለም፡፡እርሱም ሰሚው ተመልካቹ ነው፡፡» (አል ሹራ 11)   

ይህ አንቀፅ በየትኛውም ሁኔታ በፍጡራንና በፈጣሪ መካከል መመሳሰል እንደሌለና አላህ ሰሚና ተመልካች መሆኑን ያሳያል፡፡ መስሚያና መመልከቻ የብዙ ፍጡራን መገለጫዎች ቢሆኑም ነገር ግን የአላህ መስሚያና መመልከቻ ከፍጡራኑ ጋር አይመሳሰልም፡፡ በመስሚያና በመመልከቻ አምሳያ እንዳሌለው ሁሉ በሌሎችም ባህሪያቱ አምሳያ የለውም፡፡  ይህ አንቀጽ ሙስሊሞች ለአላህ የማይገቡ ባህሪያትን ከመረዳት አንጻር ሊኖራቸው ለሚገባው ትክክለኛ አካሄድ በመርህ መልክ ይቀርጻል።  አንቀጹ የጉድለት ባህሪዎችን ጥቅል በሆነ መልኩ ዉድቅ ሲያደርግ ምሉዕ ባህሪዎችን ግን በዝርዝር ያጸድቃል።

   አቅጣጫዎች ህዋሳዊ ማነጻጸሪያ reference point በመጠቀም ብቻ የሚታወቁ ናቸው። ማንኛውም ሰው የቂብላን አቅጣጫ ለማወቅ ጸሀይን ማነጻጸሪያ እንደሚያደርገው ማለት ነው። ሰዎች በአዕምሮአቸው የሚቀርጿቸው ማነጻጸሪያዎች ሁሉ በፍጥረተ አለሙ የተገደቡ በመሆናቸው ስለአላህ ለመናገር እነዚህን ፍጡራዊ ማነጻጸሪያዎችን መጠቀም አይገባም።

፨ አህሉሱና ፍልስፍዎችን በቁርአን እና በሱና ላይ አይሾሙም። አላህ ለራሱ ያጸደቃቸውን ባህሪዎች ያጸድቃሉ፤ ለአላህ ተገቢዉን ክብር ስለሚሰጡ ስለባህሪዎቹ የተነገሩ መረጃዎችን የፍጡራንን ባህሪ በሚረዱበት ሁኔታ አይረዱም። ሁልጊዜ መነሻቸው አላህን ከጉድለትና ከመመሳሰል ማጽዳት ስለሆነም እነዚህና መሰል የአስተሳሰብ ግድፈቶች አይገጥሟቸውም ።
አዎን! አላህን በጉድለትም ይሁን ከፍጡራን ጋር በመመሳሰል ከመግለፅ የፀዱ ናቸው።

በአንፃሩ አህባሾችና አርአያዎቻቸው ጀህሚዮች ግን ሁሌም መነሻቸው ስለ አላህ የተነገሩ መረጃዎችን ልክ ፍጡራን ላይ በሚያውቋቸው ባህሪያት መልኩ መረዳት ስለሆነ አላህን ከፍጡራን መለየት ያልቻሉ "ሙመሲላህ" አመሳሳዮች እነሱው ናቸው።

የሰማያትና የምድር ፈጣሪ አምላክ ሰለሆነው አላህ ሲነገር እንዴት ፍጡራዊ የሆኑ ባህሪዎች ይታወሳሉ??

አላህ ከጥመት ይጠብቀን!

አቡጁነይድ
ዙልቂእዳ 17/1436 ዓ.ሂ

No comments:

Post a Comment